አትተኙ!
እስቲ ስንቶቻችሁ ናችሁ “የሕይወቴ ቅኝት” የሚለውን መጽሐፍ ያነበባችሁ? ያላነበባችሁ እንግዲህ ተዋውሳችሁ አንብቡ ምክንያቱም ሁለተኛ እትም ለማሳተም “እቁብ ግቡልኝ?” ብዬ ጓደኞቼን በዚህ ዘመን አላስቸግርም፡፡ ድሮ የእኛ ዘመን፣ የእነሱ ዘመን ስንል አስር ወይንም ሃያ ዓመት ልዩነት እየፈለግን ነበር፤ ምክንያቱም ለውጦች አዝጋሚ (evolutional change) ናቸዋ፡፡ አሁን እኮ ዘመን ወደ ሳምንት ተቀይሯል መሰለኝ ባለፈው ሳምንት የነበረ ዛሬ ተለውጦ ታገኙታላችሁ፡፡ ነገር ሁሉ እንደቤት አስቤዛ ተለዋዋጭ ሆኗል፡፡ የዛሬ ሦስት ዓመት በኤውብ እቁብተኞቼ ድጋፍ አሳትሚያለሁ፡፡ እና ኑሮ ቀልብ ባሳጣበት እና አንባቢ በጠፋበት በዚህ ዘመን ወደ ማተምያ ቤት አልሄድም ለማለት ነው፡፡ ለማንኛውም መጽሐፌን ያነሳሁላችሁ ከዚያ ውስጥ አንዱን ሰበዝ መዝዤ ላወራላችሁ ፈልጌ ነው፡፡









