እኩልነት ለምኔ!
የማርች ወር መቼስ ሴቶች በአንድ ጣራ ስር በብዛት የምንታደምበት ወር ነው፡፡ ደስ ያሰኛል! ቢያንስ በአመት እንዲህ አምሮብን፣ ተሳክቶልን፤ በጀት ተበጅቶልን (ውሳኔ ሰጪው በአብዛኛው ያኛው ጾታ ነው ብዬ ነው) የልብ የልባችንን ማውራት ቀላል ነገር እንዳይመስላችሁ፡፡ በዚህ አጋጣሚ አቅልላችሁ ለተመለከታችሁት ወንድሞች እና እህቶች ይቅር በሉኝና ተሳስታችኋል የምል ነኝ (ስለይቅርታችሁ አመሰግናለሁ!)፡፡ አንዳንዶችማ “በየአመቱ ተመሳሳይ ነገር ለማውራት ቢሰበሰቡት ምን ዋጋ አለው፣ ከስብሰባ ያለፈ ተግባር አናይም፣ ለይስሙላ ነው፣ ወዘተ” በሚል መንፈስ ድከም ብሏቸው ሌላውንም ሰው ያዳክማሉ፡፡









